Publisher's Synopsis
ሐዋርያቱ የተቀበሉት ተልዕኮ በዋናነት ፍሬያማና ዉጤታማ ሊሆን የሚችለዉ በምድራዊና ሰብአዊ ጥበብና ብርታት ሳይሆን በመለኮታዊ ኃይል አብሮነት ብቻ መሆኑን የጠራቸዉ ጌታ በጥብቅ አስገንዝቧቸዋል፡፡ በኢየሩሳሌም፣ በይሁዳ፣ በሰማርያና እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ የእርሱ እዉነተኛ ምስክሮችና አገልጋዮች ይሆኑ ዘንድ ጌታም መለኮታዊዉን ኃይል እስኪቀበሉ በኢየሩሳሌም አንዲጠብቁ አዘዛቸዉ፡፡ እነርሱም በቁጥር መቶ ሃያ የሚያህሉ ሆነዉ በአንድነት በጾም በጸሎት የተስፋውን ቃል በመጠባበቅ ላይ ሳሉ በዓለ ሃምሳ ቀን ድንገት ታላቅ ክስተት እንደሆነ ሉቃስ ዘግቦታል (የሐዋርያት ሥራ 2፡ 2-4)፡፡የመጀመሪያዋ ቤተክርስቲያን በኢየሩሳሌምና በአካባቢዋ ተመሰረተች፡፡ አገልጋዮች በተቀበሉትና በተሞሉት መለኮታዊ ኃይል ታላቁን የመዳን ወንጌል የምስራች እየሰበኩ ዞሩ ፤ ጌታም ከእነርሱ ጋር ይሰራ ነበር፡፡ ዛሬም በምድር ያለችዉ ቤተክርስቲያን የተሰጣትን ታላቁን ተልዕኮ በተገቢዉ መንገድ መወጣት ይቻላት ዘንድ በቅድሚያ ከመለኮታዊዉ ኃይልና ሥልጣን ጋር መገናኘት አለባት፡፡ የጨለማዉን መንግስትና ኃይል በመገርሰስ በልዩ ልዩ መንገድ ታስረዉ የተጨቆኑትን ነጻ ለማዉጣትና የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀመዛሙርት ለማድረግ፣ ተተኪና ተራማጅ መሪዎችን በማፍራት ዉጤት ለማስገኘት ፤በመጀመሪያዋ ቤተክርስቲያን በግልጽ ይሰራ በነበረዉ መለኮታዊ ኃይል መሞላትና መታጠቅ አስፈላጊ ነዉ፡፡